Tuesday, July 19, 2011

Amharic Poem by Ashagrew

አለ ልባል ብቻ አልኖርም
አለህ አንተ እኮ እንዲህ ነህ ተብዬ
ለመከበር ለመሞካሸት ብዬ
አልኖርም
ራሴን እየደለልሁ ወገኔን አላታልም
ሥራዬ ካልተናገረ
ተግባሬ ካልመሰከረ
ድርጊቴ እኔን ካላስከበረ
አለ እየተባልኩ ሳልኖር
ጠቢብ ስባል ሳልማር
በከንቱ ውዳሴ ስቆለጳጰስ ከምኖር
ስጋዬ ይበስብስ ልሙት በቃ ልረሳ
ስሜ ብቻ በሰራሁት መልካም ይነሳ
በዚህች ከንቱ ዓለም
በሸር ተንኮል ከምፍገመገም
ጥንቅር ብዬ ልቅር ልጥፋ
ለባዘነው ወገኔ ካልሆንኩ ተስፋ
መኖሬ ካልሆነ ለሌላው ቤዛ
ለተራበ ለተጠማው መንፈሴ ካልተገዛ
ያቅሜን ካላደረግሁ
የምችለውን ካልሰጠሁ
በእሾህ ጋሬጣ እየተወጋ
ቀን ከሌሊት እየፈጋ
ሳይኖረው ለሰጠኝ
ሳይደላው እዚህ ላደረሰኝ
ህሊናዬ ምን መልስ አለው
ምን ብዬ በምን ውስጤን ልደልለው
የኔ መኖር ትርጉም የለው
ከራሴ ጋር ስዋጋ ከምኖር
ልሙት በቃ ልቀበር
ነጭ ለብሼ ስወደስ ተከሽኜ
ያላደረግሁትን ያልሆንሁትን ሆኜ
ከምውገረገር
ከመሸበት ልደር
እውነት ተናግሬ
ለቀናነት መስክሬ
ደካማ ወገኔ ጋር አብሬ
ያለኝን አካፍዬ
ክስት ሆኖ ሥራዬ
ማንነቴ ይገለጽ እኔነቴ ይታወቅ
ምግባሬ ይቃና ሥርዓቴም ይታረቅ
አለ ልባል ብቻ አልኖርም
ባልሰራሁት አልከብርም
ባልሁንኩት አልወደስም
መኖሬ ምክኒያት ይኑረው
እኔን እኔ እንድወደው።
    ከአሻግረው

No comments:

Post a Comment